Saturday, August 23, 2014

የአቶ ኤርሚያስ አመልጋ የመመለስ ጥያቄን መንግሥት እየመከረበት ነው

 የአክሰስ ሪል ስቴትን ጉዳይ እንዲመለከት የመንግሥት ከፍተኛ ባለሥልጣናትና የሪል ስቴቱ ደንበኞች ተወካዮችን በአባልነት አቅፎ የተቋቋመው ዓብይ ኮሚቴ፣ ለመጀመርያ ጊዜ የተፈጠረውን ችግር ማየት ጀመረ፡፡

የአክሰስ ሪል ስቴት መሥራችና ሊቀመንበር አቶ ኤርሚያስ አመልጋ ወደ አገር ለመመለስ ያቀረቡትን ጥያቄ እየመከረበት ነው፡፡

የሪፖርተር ምንጮች እንደገለጹት፣ የአክሰስ ሪል ስቴትን ጉዳይ እንዲመለከት የተዋቀረው ዓብይ ኮሚቴ የመጀመሪያውን ይፋ ስብሰባ ያደረገው ባለፈው ዓርብ ነሐሴ 16 ቀን 2006 ዓ.ም. ነበር፡፡

በንግድ ሚኒስቴር ተወካይ የሚመራው ዓብይ ኮሚቴ በመጀመሪያው ስብሰባው አቶ ኤርሚያስ አመልጋ ወደ አገር ተመልሰው ኩባንያውን እንደገና ለማስቀጠል አቅርበውታል በተባለው ተደጋጋሚ ጥያቄ ላይ መወያየቱ ታውቋል፡፡


አቶ ኤርሚያስ አክሰስ ሪል ስቴት የገጠመውን ችግር ለመፍታትና በአገር ውስጥ ሆነው ለመሥራት ለጠቅላይ ሚኒስትሩ ጭምር በደብዳቤ ገልጸው እንደነበር የሚጠቁሙት ምንጮች፣ በአክሰስ ሪል ስቴት ዙሪያ ከዚህ በኋላ መወሰድ የሚኖርበት ዕርምጃ ምን መሆን እንዳለበት ውይይት ተደርጐበታል ብለዋል፡፡

በጉዳዩ ላይ በቀጥታ መንግሥት ጣልቃ በመግባት መፍትሔ ሊሆን የሚችለውን ዕርምጃ ለመውሰድ እንዲያስችል፣ ከተለያዩ መንግሥታዊ መሥሪያ ቤቶች አክሰስ ሪል ስቴትን የሚመለከቱ መረጃዎች ተጠናክረው ለኮሚቴው እንዲቀርቡ ተወስኗል፡፡

ለዓብይ ኮሚቴው ይቅረቡ የተባሉ መረጃዎችን በመያዝ መፍትሔ ይሆናል የተባለውን ውሳኔ እስከ ነሐሴ 30 ቀን 2006 ዓ.ም. ድረስ ለመወሰን ስምምነት ላይ መደረሱን ምንጮች ያስረዳሉ፡፡

አቶ ኤርሚያስ ወደ አገር ቤት ተመልሰው ችግሩን ለመፍታት እንደሚችሉ፣ ይህንንም ለማድረግ አስፈላጊውን ዝግጅት ማድረጋቸውንና ለዚህም ዋስትና እንዲሰጣቸው በደብዳቤ አቅርበዋል የተባለውን ጥያቄያቸውን ተከትሎ፣ ጉዳዩ የሚመለከታቸው አካላት ከአቶ ኤርሚያስ ጋር ንግግር ሳይጀምሩ እንዳልቀረ እየተነገረ ነው፡፡

ሆኖም አቶ ኤርሚያስ ወደ አገር ተመልሰው እንዲሠሩ የሚፈቀድ ከሆነ በሕግ አግባብ ያስኬዳል አያስኬድም የሚለውን ጉዳይ ይኼው ዓብይ ኮሚቴ እንደተነጋገረበትም ምንጮች ለሪፖርተር ገልጸዋል፡፡ በተለይም የአክሰስ ሪል ስቴት ተጐጂዎች ይህንን ሐሳብ እንዴት ይቀበሉታል የሚለውም ሌላው አነጋጋሪ ጉዳይ ነበር ተብሏል፡፡  

ለዓብይ ኮሚቴው መዋቀር ዋና ምክንያት የአክሰስ ሪል ስቴት ደንበኞች ችግሩን በተመለከተ መንግሥት ጣልቃ ገብቶ መብታቸውን እንዲያስጠብቅላቸው ባቀረቡት ጥያቄ መሠረት ነው፡፡ መንግሥትም ጉዳዩን በማየት ዓብይ ኮሚቴው እንዲዋቀር ያደረገ ቢሆንም፣ ኮሚቴው ብዙም ሳይንቀሳቀስ በመቅረቱ በቤት አሠሪዎች ዘንድ ቅሬታ ፈጥሮ ቆይቷል፡፡

አሁን እየተደረገ ያለው እንቅስቃሴ ግን መንግሥትም ለጉዳዩ ትኩረት እየሰጠ መሆኑን የሚያሳይ እንደሆነ፣ ሊወሰድ የሚችለውን ውሳኔ ለመወሰን ግን ከባድ ሊሆን ይችላል የሚል ሥጋት አለ፡፡ በተለይ ከአክሰስ ሪል ስቴት ቤት አሠሪዎች በተጨማሪ አክሰስ ሪል ስቴት ላይ ገንዘብ አለን የሚሉ ወገኖች መኖራቸው ጉዳዩን ይበልጥ እንዳወሳሰበው ምንጮች አመልክተዋል፡፡

እስከ ነሐሴ 30 ቀን 2006 ዓ.ም. ዓብይ ኮሚቴው ይወስናል ተብሎ የሚጠበቀው ውሳኔ የአክሰስ ሪል ስቴትና የደንበኞቹ ዕጣ ፈንታ ምን ሊሆን እንደሚችል ያመላክታል ተብሎም እንደሚጠበቅ ተጠቁሟል፡፡

ጉዳዩን እንዲመለከቱ በዓብይ ኮሚቴ ውስጥ እንዲካተቱ የተደረጉት ንግድ ሚኒስቴር፣ የቤቶች፣ ከተማ ልማትና ኮንስትራክሽን ሚኒስቴር፣ የፌዴራል ፖሊስ፣ የውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር፣ የፍትሕ ሚኒስቴር፣ የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር፣ የሰነዶች ማረጋገጫና ምዝገባ ጽሕፈት ቤት የሪል ስቴቱ ደንበኞች ተወካዮች ናቸው፡፡

ቁጥራቸው ከሁለት ሺሕ በላይ የሆኑ ኢትዮጵያውያንና ትውልደ ኢትዮጵያዊያን አክሰስ ሪል ስቴት የመኖሪያ ቤት እንዲገነባላቸው ገንዘብ ከፍለው፣ በውሉ መሠረት ሳያስረክባቸው አቶ ኤርሚያስ ከአገር መውጣታቸው ይታወሳል፡፡ በወቅቱ አቶ ኤርሚያስ በርካታ ደረቅ ቼኮች እየፈረሙ ገንዘባቸው እንዲመለስላቸው ለሚፈልጉ ደንበኞች በመስጠታቸው ምክንያት፣ በተለይ በአንድ ግለሰብ ክስ ተመሥርቶባቸው ነበር፡፡

ተጎጂዎች በመሰባሰብ ለመንግሥት አቤት በማለታቸው መንግሥትም ሕጋዊና አስተዳደራዊ መፍትሔ ለመስጠት ጉዳያቸውን ከፍተኛ የመንግሥት ባለሥልጣናት የተካተቱበት ኮሚቴ በማዋቀር ጭምር ሲከታተለው እንደነበር መዘገባችን አይዘነጋም፡፡
http://www.ethiopianreporter.com/

No comments:

Post a Comment