Tuesday, February 25, 2014

በአርሲ ዞን የተጣራ ወርቅ ክምችት በአንድ አርሶ አደር ተገኘ


አዲስ አበባ ፣ የካቲት 18 ፣ 2006 (ኤፍ.ቢ.ሲ.) በአርሲ ዞን ሱዴ ወረዳ አቡኩይ ቡርቂቱ በተባለች ወረዳ በመሬት ውስጥ ለበርካታ አመታት ተቀብሮ የቆየ የተጣራ የወርቅ ክምችት ተገኘ።

የተጣራው የወርቅ ክምችቱ የተገኘው አቶ ወርቁ ለሚ በተባሉ የአካባቢው ነዋሪ እንደሆነ የኦሮሚያ ሬዲዮና ቴሌቪዥን ድርጅት ዘግቧል።

ከወርቅ ክምችቱ ጋር ተቀብሮ የቆየ የሰው አጽምም መገኘቱን ነው ዘገባው የጠቆመው።

እንደዚህ አይነት የማዕድን ክምችት ሲገኝ 40 በመቶው ላገኘው ሰው፣ 40 በመቶው ለፌዴራል መንግስትና 20 በመቶው ደግሞ ለክልሉ መንግስት እንደሚከፋፈል ተመልክቷል።

የቀበሌዋ ነዋሪ አቶ ወርቁ ለሚ ካገኙት ድርሻቸው ውስጥ 10 በመቶውን ለወረዳቸው አበርክተዋል።


የኦሮሚያ ውሃ ማዕድንና ኢነርጂ ቢሮ ኃላፊ አቶ ሞቱማ መቃሳ እንዳሉት፥ የማዕድናትን ህግ መሰረት በማድረግ አንድ ግለሰብ ወይም ድርጅት የማዕድን ክምችት ካገኘ ለቢሮው በማስታወቅ ይመረመራል።

አቶ ወርቁ ያገኙት የተጣራ ወርቅም በዚህ መስፈርት ውስጥ ያለፈ መሆኑን ኃላፊው አረጋግጠዋል።

የወርቅ ክምችቱ ቀደም ሲል በአካባቢው እንዳልነበረና ከሌላ አካባቢ ተወስዶ የተቀበረ እንደሆነ በጥናት መረጋገጡንም ነው  አቶ ሞቱማ የተናገሩት።

የወርቅ ክምችቱን ምናልባትም በጣሊያን ወረራ ወቅት በአካባቢው ሳይቀበር እንዳልቀረም ተጠርጥሯል።

የወርቅ ክምችቱ ምን ያህል እንደሆነ በጥናት የሚረጋገጥ እንደሆነም አቶ ሞቱማ ጠቁመዋል።

ከአርኪኦሎጂ ባለሙያዎችና ጉዳዩ ከሚመለከታቸው ምሁራን ጋር በመሆን ተጨማሪ ምርመራ በቀጣይ ይካሄዳል ተብሏል።
http://www.fanabc.com/

No comments:

Post a Comment