Thursday, February 13, 2014

የግብፅ ሚኒስትር የግድቡ ግንባታ እንዲቆም በመጠየቃቸው ውይይቱ ተቋረጠ



የግብፅ የውኃና መስኖ ሚኒስትር መሐመድ አብዱል ሙታሊብ ከኢትዮጵያ አቻቸው ጋር የሁለትዮሽ ውይይት ለማድረግ በጠየቁት መሠረት ባለፈው ሰኞ አዲስ አበባ ቢገቡም፣ የታላቁ ህዳሴ ግድብ ግንባታ እንዲቆም በመጠየቃቸው ውይይቱ በሰዓታት ውስጥ ተቋረጠ፡፡

የግብፅ ሚኒስትር ከኢትዮጵያ አቻቸው አቶ አለማየሁ ተገኑና ከባልደረቦቻቸው፣ እንዲሁም ከውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር ከተወከሉ ባለሙያዎች ጋር ባለፈው ሰኞ መገናኘታቸውን ለማወቅ ተችሏል፡፡

በታላቁ የኢትዮጵያ ህዳሴ ግድብና ተያያዥ የፖለቲካ ጉዳዮች ላይ የመንግሥት ኮሙዩኒኬሽን ጉዳዮች ጽሕፈት ቤት ከጋዜጠኞች ጋር ለመወያየት ባዘጋጀው መድረክ ላይ የተገኙት አቶ አለማየሁ ተገኑ፣ የግብፅ አቻቸው ሁለት አጀንዳዎችን ይዘው መቅረባቸውን ተናግረዋል፡፡

የግብፅ ሚኒስትር በስልክ ደውለው ወደ አዲስ አበባ ለመምጣትና ለመወያየት ባቀረቡት ጥያቄ መሠረት መገኘታቸውንና ይዘው የመጡዋቸው አጀንዳዎችም ከዚህ ቀደም ተቀባይነት ሊያገኝ ያልቻለውን የዓለም አቀፍ ባለሙያዎች ቡድን ተጨማሪ ጥናት እንዲያከናውን የሚጠይቅ፣ እንዲሁም በግንባታው ላይ መተማመንን ማጐልበት የሚሉ ጉዳዮች መሆናቸውን ጠቁመዋል፡፡



የዓለም አቀፍ ባለሙያዎች ቡድንን በተመለከተ ኢትዮጵያና ሱዳን እንደማይቀበሉት ከዚህ ቀደም መገለጹንና አሁንም ይህንን አቋም በድጋሚ እንዲገነዘቡት መደረጉን አቶ አለማየሁ አስረድተዋል፡፡

በግድቡ ግንባታ ላይ መተማመንን ማጐልበት በሚል በግብፅ በኩል በቀረበው ሐሳብ ውስጥ የቀድሞው የግብፅ የውኃ መጠን እንደማይቀንስ ኢትዮጵያ እንድታረጋግጥ የሚጠይቅ መሆኑን ሪፖርተር ያገኛቸው መረጃዎች ያመለክታሉ፡፡ ይህንን በተመለከተ በሰኞው ስብሰባ የግብፁ ሚኒስትር በድጋሚ አንስተው ኢትዮጵያ እንደማትቀበለው ግልጽ እንደተደረገላቸው አቶ አለማየሁ በውይይት መድረኩ ላይ ለተገኙ ጋዜጠኞች ገልጸዋል፡፡

ይህንን የኢትዮጵያ አቋመ ጽኑነት የተረዱት የግብፅ የውኃ ሀብት ሚኒስትር ዓለም አቀፍ ውይይቱን ለመቀጠልና ከሦስቱ አገሮች በሚወከሉ ባለሙያዎች የቀድሞዎቹ ባለሙያዎች ያቀረቧቸው ምክረ ሐሳቦች ተግባራዊ እንዲደረጉ፣ የግድቡ ግንባታ ይቁም ብለው መጠየቃቸውን አቶ አለማየሁ አስረድተዋል፡፡

‹‹ያነሷቸው ጥያቄዎች በጭራሽ በኢትዮጵያ በኩል ተቀባይነት እንደማይኖራቸውና የግድቡ ግንባታም ለሰከንዶች እንደማይቆም ካስረዳናቸው በኋላ ምሳ ጋብዘናቸው በሦስት ሰዓታት ውስጥ ተለያይተናል፤›› ሲሉ አቶ አለማየሁ ገልጸዋል፡፡

በዚህ ውይይት ላይ ግብፆች በዓባይ ወንዝ ፖለቲካና በግድቡ ላይ እየፈጠሩ ያለውን ጫና በተመለከተ ከጋዜጠኞች ለተሰነዘሩ ጥያቄዎች በሰጡት ምላሽ፣ ከሁለት ዓመታት በፊት ግንባታው ሊጀመር ለነበረው የጨሞጋ የዳ የኃይል ማመንጫ ግድብ ቻይና የፈቀደችውን ብድር ግብፆች ማስከልከላቸውን ሚኒስትሩ ገልጸዋል፡፡

በመቀጠልም የህዳሴው ግድብ ከተጠናቀቀ በኋላ ለኃይል ማስተላለፊያ ፕሮጀክት የሚውል 1.2 ቢሊዮን ዶላር ብድር ለኢትዮጵያ በቅርቡ በቻይና መንግሥት መፈቀዱን ተከትሎ፣ ተጨማሪ ጫና በማድረግ ግብፆች ብድሩ እንዳይለቀቅ ጥረት ቢያደርጉም ሳይሳካ መቅረቱን ተናግረዋል፡፡ ‹‹ግብፆች ጩኸታቸውንና በር ማንኳኳታቸውን ይቀጥሉ፡፡ እኛ ሥራችንን እንቀጥላለን፤›› ሲሉ ሚኒስትሩ የሚደረገውን ጥረት ውጤት አልባነት ገልጸዋል፡፡

አሁን በመገንባት ላይ የሚገኘው የጊቤ ሦስት ኃይል ማመንጫ ፕሮጀክት የብድር ጥያቄ ለአፍሪካ ልማት ባንክና ለዓለም ባንክ ቀርቦ እንደነበር፣ ነገር ግን በተለያዩ አካላት ተፅዕኖ ባንኮቹ ውሳኔ መስጠት መቸገራቸውን ሚኒስትሩ አስታውሰዋል፡፡ ይህ መጓተትና የተፅዕኖው መብዛት ምክንያቱ የገባቸው የቀድሞው ጠቅላይ ሚኒስትር መለስ ዜናዊ የብድር ጥያቄው እንዲቋረጥ አድርገው፣ በአገሪቱ አቅም እንዲገነባ መወሰናቸው ተፅዕኖ ለመፍጠር የሞከሩትን ወገኖች እንዳሸበረ ገልጸዋል፡፡ ይህንን ሁኔታ በማስታወስም ‹‹የህዳሴውን ግድብ ጠላቶች መምታት የሚቻለው በራሳችን አቅም ላይ ስንተማመንና ስንተባበር ነው፤›› ብለዋል፡፡

የግድቡ ግንባታ በግብፅ ላይ የሚፈጥረው ጉዳት የለም ወይ በሚል ለቀረቡ ጥያቄዎች ምላሽ የሰጡት በውኃ መስኖና ኢነርጂ ሚኒስቴር የወሰንና ወሰን ተሻጋሪ ወንዞች ዳይሬክቶሬት ዳይሬክተር አቶ ፈቅአህመድ ነጋሽ፣ ‹‹ጉዳት አለው›› ብለዋል፡፡ ‹‹ዋናው ነገር ጉዳቱ ጉልህ ነው አይደለም የሚለው ነው መመለስ ያለበት፤›› የሚሉት አቶ ፈቅአህመድ፣ የአስዋን ግድብ አሁን ከ200 ሜጋ ዋት በላይ እንደሚያመነጭና የህዳሴው ግድብ እውን ሲሆን ግን በስድስት በመቶ ሊቀንስ እንደሚችል፣ ይህ ማለት ደግሞ ጉልህ ጉዳት እንዳልሆነ አስረድተዋል፡፡
http://www.ethiopianreporter.com

No comments:

Post a Comment