Monday, August 12, 2013

የከባድ ሙስና ወንጀል ተጠርጣሪዎች ምርመራ ተጠናቆ ለክስ ተቀጠሩ

- አቶ እሸቱ ወልደሰማያትን ጨምሮ አሥር ተጠርጣሪዎች በዋስ ተለቀቁ 




በተጠረጠሩበት ከባድ የሙስና ወንጀል ከግንቦት 2 ቀን 2005 ዓ.ም. ጀምሮ ላለፉት ሦስት ወራት፣ ለሰባት ጊዜያት ተጨማሪ የምርመራ ጊዜ እየተጠየቀባቸው በምርመራ ላይ የከረሙት አቶ መላኩ ፈንታና አቶ ገብረዋህድ ወልደጊዮርጊስን ጨምሮ የ33 ተጠርጣሪዎች የምርመራ ጊዜ በመጠናቀቁ፣ በሚቀጥሉት 15 ቀናት ውስጥ ክስ እንዲመሠረት ፍርድ ቤት አዘዘ፡፡ የፌዴራል ከፍተኛ ፍርድ ቤት ሁለተኛ ወንጀል ችሎት ነሐሴ 3 ቀን 2005 ዓ.ም. ትዕዛዙን ያስተላለፈው፣ የፌዴራል የሥነ ምግባርና የፀረ ሙስና ኮሚሽን መርማሪ ቡድን በተጠርጣሪዎቹ ላይ ምርመራውን አጠናቆ፣ ነሐሴ 3 ቀን 2005 ዓ.ም. ለኮሚሽኑ ዓቃቤ ሕግ ማስረከቡን ለችሎቱ ሲያሳውቅ ነው፡፡ ላለፉት ሦስት ወራት በተጠርጣሪዎቹ ተፈጽመዋል ስለተባሉት የተለያዩ የሙስናና የአራጣ ክሶችን ማቋረጥ፣ የተለያዩ ሸቀጣ ሸቀጦችና ዕቃዎች ሳይቀረጡ እንዲገቡ ማድረግ፣ ግብር መሰወር፣ ግብር አሳንሶ መገመት፣ በተከለከለ የፍራንኮ ቫሉታ ፈቃድ ሲሚንቶ ማስገባት፣ ከቀረጥ ነፃ የገቡ የተለያዩ ዕቃዎችን እንዲገቡ ከተደረገበት ዓላማ ውጭ መጠቀምና ሌሎችም በርካታ ምርመራዎች እየተደረጉ እንደነበር መዘገባችን ይታወሳል፡፡

በመሆኑም መርማሪ ቡድኑ ምርመራውን ማጠናቀቁንና መዝገቡን ክስ ለሚመሠርተው የኮሚሽኑ ዓቃቤ ሕግ ማስረከቡን ለችሎቱ አስረድቷል፡፡ መርማሪ ቡድኑ በተጠረጠሩበት የሙስና ወንጀል በተለያዩ ስድስት ፋይሎች በመከፋፈል ሲመረምር መክረሙን በማስታወስ መዝገቡን ለከሳሹ ዓቃቤ ሕግ ሲያስረክብ፣ ከስድስቱም የምርመራ መዝገቦች አሥር ተጠርጣሪዎችን በዋስ መልቀቁን ለችሎቱ አስታውቋል፡፡ በዚህም መሠረት በአቶ መላኩ ፈንታ መዝገብ ሥር የሚገኙትን የኢትዮጵያ ገቢዎችና ጉምሩክ ባለሥልጣን የዓቃቢያነ ሕግ ዳይሬክቶሬት ዋና ዳይሬክተር አቶ እሸቱ ወልደሰማያትንና የተጠርጣሪ መርክነህ ዓለማየሁ እህት ወይዘሮ ትዕግሥት አለማየሁን በዋስ ለቋል፡፡ በአቶ ገብረዋህድ ወልደጊዮርጊስ የምርመራ መዝገብ የባለሥልጣኑ የወንጀል ምርመራ ዳይሬክቶሬት ዳይሬክተር አቶ ተወልደ ብስራትን በዋስ ለቋል፡፡
 በአቶ መሐመድ ኢሳ የምርመራ መዝገብ አቶ ዳኜ ስንሻውንና ወይዘሮ ፍሬሕይወት ጌታቸው፣ በእነ ጥጋቡ ግደይ የምርመራ መዝገብ የእልፍኝ ቆርቆሮ ፋብሪካ ባለቤት አቶ ባሕሩ አብርሃን፣ በእነ መልካሙ እንድሪስ የምርመራ መዝገብ የዋው ትራንዚት ባለቤት ወይዘሮ አልማዝ ከበደን፣ በእነ ተመስገን ሥዩም የምርመራ መዝገብ አቶ ኃይለ ማርያም አሰፋና አቶ ሥዩም ለይኩን የተባሉ ተጠርጣሪዎች በዋስ ተለቀዋል፡፡ መርማሪ ቡድኑ ለፍርድ ቤቱ ሌላው ያቀረበው ጥያቄ፣ ንብረታቸው በኦዲት እየተመረመረ የሚገኙት አቶ ነጋ ገብረ እግዚአብሔር፣ አቶ ከተማ ከበደ፣ አቶ ስማቸው ከበደና አቶ ምህረተአብ ቀሪዎቹ 33 ተጠርጣሪዎችን በሚመለከት ነሐሴ 3 ቀን 2005 ዓ.ም. የምርመራ መዝገቡን የተረከበው የኮሚሽኑ ዓቃቤ ሕግ ለፍርድ ቤቱ ባቀረበው ማመልከቻ፣ ክስ እስከሚመሠርት ድረስ በሕጉ መሠረት 15 ቀናት እንዲፈቀድለትና እስከዚያው ድረስ ተጠርጣሪዎቹ በማረሚያ ቤት እንዲቆዩለት ጠይቋል፡፡ ተጠርጣሪዎቹ በማረሚያ ቤት እንዲቆዩ የኮሚሽኑ ዓቃቤ ሕግ የጠየቀበትን ምክንያት ሲያስረዳ፣ ተጠርጣሪዎቹ የተጠረጠሩበት ወንጀል በፀረ ሙስና አዋጅ ቁጥር 434(1) መሠረት የሚመሠረትባቸው ክስ ከአሥር ዓመታት በላይ ሊያስቀጣ ስለሚችልና ዋስትና የሚከለክል በመሆኑ ነው፡፡ የተጠርጣሪዎቹ ጠበቆች የኮሚሽኑ ዓቃቤ ሕግ ያቀረበውን ጥያቄ በከፍተኛ ሁኔታ ተቃውመውታል፡፡ ተቃውሟቸውንም ሲገልጹ የኮሚሽኑ ዓቃቤ ሕግ መዝገቡ በደረሰው ዕለት ምንም ሳይመረምር ዋስትና ይከልክል ወይም አይከልክል ሳያውቅ በአዋጅ ቁጥር 434(1) መሠረት ዋስትና መከልከል አለበት ማለቱን ነው፡፡ አዋጁ ሊከለክል የሚችለው ክስ ሲመሠረት እንጂ ገና ለገና ይከለክላል በሚል የደንበኞቻቸውን መብት ማሳጣት እንደሌለበት ተናግረዋል፡፡ የአቶ ነጋ ገብረ እግዚአብሔር ጠበቃ በበኩላቸው ባቀረቡት መቃወሚያ፣ ደንበኛቸው ከአገር እንዳይወጡና ኦዲት የሚደረግበት ድርጅት አካባቢ እንዳይሄዱ በማገድ በዋስ እንዲወጡ ጠይቀዋል፡፡ የኮሚሽኑ ዓቀቤ ሕግ የተጠርጣሪዎቹ ጠበቆች ያቀረቡትን ተቃውሞ በመቃወም ባቀረበው መከራከሪያ ነጥብ፣ አዋጅ 434(3) እና (4) እንደሚከለክል በመጥቀስ ጥያቄያቸው ውድቅ እንዲደረግ ጠይቋል፡፡ የግራ ቀኙን ክርክር ያደመጠው ፍርድ ቤቱ የተጠርጣሪዎቹን ዋስትና ውድቅ በማድረግ፣ የኮሚሽኑ ዓቃቤ ሕግ ነሐሴ 15 እና 16 ቀን 2005 ዓ.ም. ክስ እንዲመሠርት አዟል፡፡ አብርሃ በፖሊስ ጣቢያ እንዲቆዩ የሚል ነው፡፡ ምክንያት ያለውም ለኦዲት ምርመራው በየቀኑ ስለሚያስፈልጉና ማረሚያ ቤቱ ስለሚርቅ መሆኑን ነው፡፡
http://www.ethiopianreporter.com

No comments:

Post a Comment