Monday, August 12, 2013

እግር ኳስ ፌዴሬሽን ያለጨረታ በከፈለው 1.3 ሚሊዮን ብር በፀረ ሙስና ኮሚሽን ጥያቄ ቀረበበት

በአፍሪካ እግር ኳስ ኮንፌዴሬሽን (ካፍ) ወጪ ሲኤምሲ አካባቢ እየተገነባ ላለው የካፍ አካዴሚ ብሔራዊ ፌዴሬሽኑ ያለጨረታ በከፈለው 74 ሺሕ የአሜሪካ ዶላር (1.3 ሚሊዮን ብር) ምክንያት፣ በፀረ ሙስና ኮሚሽን ጥያቄ እንደቀረበበት ምንጮች ለሪፖርተር ገለጹ፡፡ ለጉዳዩ እንግዳ የሆኑና የተደናገጡ የፌዴሬሽኑ ሥራ አስፈጻሚ ኮሚቴ አባላት፣ ፀረ ሙስና ኮሚሽን በጠየቀው ማብራሪያ ላይ ተነጋግረው ውሳኔ ላይ ለመድረስ ባለፈው ዓርብ በፌዴሬሽኑ ጽሕፈት ቤት ቢሰባሰቡም፣ ፕሬዚዳንቱ ባለመገኘታቸው ምክንያት ያለ ውጤት መበተናቸው ተሰምቷል፡፡

 እንደ ምንጮቹ የፌዴራሉ ፀረ ሙስና ኮሚሽን የኢትዮጵያ እግር ኳስ ፌዴሬሽን ስለቀረበበት የጨረታ ጉዳይ ማብራሪያ እንዲሰጠው በቁጥር 42-9/መ.መ/መ9.7314 በቀን 04/10/2005 ዓ.ም. በጻፈው ደብዳቤ እንደሆነም ይገልጻሉ፡፡ የፌዴሬሽን ምንጮች አክለው እንዳስረዱት፣ ከጥቂት ወራት በፊት የአፍሪካ እግር ኳስ ኮንፌዴሬሽን (ካፍ) ፕሬዚዳንት ሚስተር ኢሳ ሐያቱ፣ በአዲስ አበባ ሲኤምሲ አካባቢ ካፍ እያስገነባው ስላለው የካፍ አካዴሚ ጉዳይ ከፌደራል ስፖርት ኮሚሽንና ከኢትዮጵያ እግር ኳስ ፌዴሬሽን አመራሮች ጋር ለመነጋገር አዲስ አበባ ተገኝተው ነበር፡፡ በውይይታቸውም ስፖርት ኮሚሽን በበላይነት በሚቆጣጠረውና በአገሪቱ የጨረታ ሕግ መሠረት ለአካዴሚው ማስፋፊያ ፕሮጀክት ጨረታ እንዲወጣና ጨረታውን ለሚያሸንፈው ተቋራጭ የሚውለው ቅድመ ክፍያ 74 ሺሕ ዶላር (1.3 ሚሊዮን ብር) ካፍ እንደሚልክ ስምምነት ላይ ደርሰው ነበር፡፡ በስምምነቱ መሠረት ካፍ ገንዘቡን ለኢትዮጵያ እግር ኳስ ፌዴሬሽን መላኩንና የኢትዮጵያ እግር ኳስ ፌዴሬሽን ፕሬዚዳንት ከስፖርት ኮሚሽን አንዳንድ አመራሮች ጋር በመነጋገር ሕጋዊ ጨረታ ሳይወጣ በፌዴሬሽኑ ማኅተም አረጋግጠው ለአንድ ግለሰብ ሥራው እንዲሰጥ ይደረጋል፡፡ የ74 ሺሕ ዶላሩ (1.3 ሚሊዮን ብር) ክፍያም ለተቋራጩ እንዲከፈል ውሳኔ ላይ ስለመደረሱ ምንጮቹ ያስረዳሉ፡፡ ይህንኑም የፌዴሬሽኑ ፋይናንስ ክፍል ታክስ ሳይደረግ ክፍያው ስለመፈጸሙ እንደሚያውቅ ጭምር ያስረዳሉ፡፡ በመጨረሻም ጉዳዩ ለፌዴራሉ ፀረ ሙስና ኮሚሽን ደርሶ ይህ ደብዳቤ ለኢትዮጵያ እግር ኳስ ፌዴሬሽን እንደተጻፈ፣ በጉዳዩም ፌዴሬሽኑና ስፖርት ኮሚሽን ተነጋግረው ማብራሪያ እንዲሰጡ ጠይቋል፡፡ ስለጉዳዩ በተለይም የፌዴሬሽኑን ፕሬዚዳንት አቶ ሳህሉ ገብረወልድን ለማግኘት የተደረገው ጥረት አልተሳካም፡፡
 http://www.ethiopianreporter.com/

No comments:

Post a Comment