Wednesday, July 10, 2013

አራጣ በማበደር ወንጀል 25 ዓመታት የተፈረደባቸው አቶ አየለ ደበላ (አይኤምኤፍ) አረፉ

አራጣ በማበደርና በሌሎችም ክሶች ከአራት ዓመታት በፊት ክስ ተመሥርቶባቸው 25 ዓመታት ተፈርዶባቸው ማረሚያ ቤት የነበሩትና በቅጽል ስማቸው ‹‹አይኤምኤፍ›› በመባል የሚታወቁት አቶ አየለ ደበላ ከዚህ ዓለም በሞት ተለዩ፡፡
በተወለዱ በ70 ዓመታቸው ሰኔ 30 ቀን 2005 ዓ.ም. ረፋዱ ላይ በእስር ላይ በሚገኙበት በአዲስ አበባ ማረሚያ ቤት ክሊኒክ ውስጥ ሕይወታቸው ማለፉ የታወቀው አቶ አየለ፣ የቀብር ሥርዓታቸው ሐምሌ 2 ቀን 2005 ዓ.ም. በመንበረ ፀባኦት ቅድስት ሥላሴ ካቴድራል ተፈጽሟል፡፡



አቶ አየለ ከፍተኛ በሆነ የስኳር ሕመምና ከፍተኛ ደረጃ ላይ በደረሰ የወንዴ ዕጢ (ፕሮስቴት) ካንሰር ሕመም በፖሊስ ሆስፒታል፣ በጥቁር አንበሳና በማረሚያ ቤት ክሊኒክ ላለፉት አራት ዓመታት ሕክምና የተከታተሉ ቢሆንም፣ ሕመሙ አገር ውስጥ ሊድን ባለመቻሉና እሳቸው ደግሞ በተወሰነባቸው የወንጀል ቅጣት ምክንያት ከአገር ወጥተው መታከም ባለመቻላቸው፣ ሕይወታቸው በእስር ቤት ሊያልፍ መቻሉን ልጆቻቸው ገልጸዋል፡፡

በ1935 ዓ.ም. በአዲስ አበባ ከተማ የተወለዱት አቶ አየለ፣ በ1959 ዓ.ም. ትዳር መሥር
ተው አራት ሴቶችና አምስት ወንዶች ልጆች ማፍራታቸውም ታውቋል፡፡

ከ16 ዓመታቸው ጀምሮ ለ50 ዓመታት በተለያዩ ንግዶች መሰማራታቸውን፣ በመንገድ ሥራ፣ በቤተ ክርስቲያን ማሳነጽ፣ በተለያዩ የልማት ሥራዎች ላይ በዋናነት በማሠራትና በመተባበር ግንባር ቀደም እንደነበሩም የሕይወት ታሪካቸው ያስረዳል፡፡ በዕድር፣ በዕቁብና በተለያዩ ማኅበራዊ ክንዋኔዎች ውስጥ በግንባር ቀደምትነት ስማቸው የሚነሳው አቶ አየለ ለበርካታ ቤተሰቦቻቸው፣ ወገኖቻቸውና ለመንግሥት ያበረከቱት አስተዋጽኦ በሕይወት ታሪካቸው ተካቷል፡፡

አቶ አየለ ደበላ (አይኤምኤፍ) ከኢትዮጵያ ብሔራዊ ባንክ ፈቃድ ሳይኖራቸው፣ የባንክን ሥራ ተክተው በሕገወጥ መንገድ (አራጣ) በማበደር፣ የገቢ ግብር አዋጅን በመተላለፍ፣ ግብር ባለመክፈል ወንጀሎችን ጨምሮ፣ በተመሠረተባቸው አሥር ክሶች ጥፋተኛ ተብለው፣ በፌዴራል ከፍተኛ ፍርድ ቤት በ22 ዓመታትና በ308 ሺሕ ብር ቢቀጡም፣ ክሱን የመሠረተባቸው የኢትዮጵያ ገቢዎችና ጉምሩክ ባለሥልጣን ዓቃቤ ሕግ ወደ ጠቅላይ ፍርድ ቤት ይግባኝ ብሎ፣ በ25 ዓመታትና በተጠቀሰው ገንዘብ እንዲቀጡ መደረጉን መዘገባችን ይታወሳል፡፡

ከአቶ አየለ ጋር ክስ ተመሥርቶባቸው ጥፋተኛ የተባሉት አቶ ከበደ ተሠራ (ወርልድ ባንክ) እና አቶ ገብረ ኪዳን በየነ (ሞሮኮ) በተመሳሳይ 25 ዓመታት እስራትና በገንዘብ ተቀጥተዋል፡፡ አቶ ሌንጫ ዘገዬ በ20 ዓመታት እስር ተቀጥተዋል፡፡ ፍርደኞቹ መንግሥትን ይቅርታ የጠየቁ ቢሆንም እስካሁን ምላሽ አለማግኘታቸው ታውቋል፡፡
http://www.ethiopianreporter.com

No comments:

Post a Comment