Sunday, February 17, 2013

አቶ ኤርሚያስ አመልጋ በፖሊስ ቁጥጥር ሥር ውለው ተለቀቁ


አክሰስ ሪል ስቴት ምርመራው ተቋርጧል አለ

የዘመን ባንክና የአክሰስ ሪል ስቴት መሥራች የሆኑት አቶ ኤርሚያስ አመልጋ ከደረቅ ቼክ ጋር በተያያዘ ተጠርጥረው አንድ ቀን በቁጥጥር ሥር ውለው ባለፈው ዓርብ ተለቀቁ፡፡
አክሰስ ካፒታል ግን በአቶ ኤርሚያስ ላይ የተጀመረው ምርመራ መቋረጡን አስታውቋል፡፡

አቶ ኤርሚያስ በቂርቆስ ክፍለ ከተማ ፖሊስ ጣቢያ ካዛንቺስ (ስድስተኛ) ማዘዣ ጣቢያ አንድ ቀን ካደሩ በኋላ ተለቀዋል፡፡ አቶ ኤርሚያስ ችግሩ የተፈጠረው ባለመግባባት መሆኑን ገልጸው፣ አሁን ግን ምርመራው ተቋርጦ ወደ ሥራ መመለሳቸውን አስታውቀዋል፡፡

አቶ ኤርሚያስ የተጠረጠሩበት ምክንያት የአክሰስ ሪል ስቴት ኩባንያ አንድ ደንበኛ ኩባንያው እሠራለሁ ያለውን ቤት ሠርቶ በወቅቱ አላስረከበኝም በማለት ገንዘባቸው እንዲመለስ ሲጠይቁ፣ አቶ ኤርሚያስ የ350 ሺሕ ብር ቼክ ይፈርሙላቸዋል፡፡



እኝህ ደንበኛ ዘመን ባንክ ሄደው በቼክ የተጻፈላቸውን ገንዘብ ማግኘት ባለመቻላቸው ወደ ክስ በመሄዳቸው ነው አቶ ኤርሚያስ በቁጥጥር ሥር የዋሉት ተብሏል፡፡

ምንጮች እንደሚገልጹት ግን፣ አካውንቱ ውስጥ ገንዘብ ነበር፡፡ ነገር ግን ሌላ የሪል ስቴቱ ደንበኛ አካውንቱን በፍርድ ቤት በማሳገዳቸው ገንዘቡን ማንቀሳቀስ አልተቻለም፡፡ አክሰስ ካሉት አካውንቶች ውስጥ በአንደኛው ከ1.7 ሚሊዮን ብር በላይ እንደነበር ሪፖርተር መረዳት ችሏል፡፡ ይህም መረጃ ለመርማሪዎቹ ቀርቦ የይከፈለኝ ጥያቄ ላነሱት ግለሰብ ገንዘቡ ተከፍሏቸዋል፡፡ ግለሰቡም ወዲያው ክሱን በማንሳታቸው ምርመራው ተቋርጦ አቶ ኤርሚያስ ተለቀዋል፡፡

አክሰስ ሪል ስቴት ለሪፖርተር በላከው መግለጫ እንዳስታወቀው፣ በአካውንቱ ውስጥ በቂ ገንዘብ መኖሩን አረጋግጧል፡፡ የተፈጠረው ክስተትም በቢዝነስ እንቅስቃሴ ውስጥ በየጊዜው የሚያጋጥም መሆኑን የገለጸው አክሰስ፣ መርማሪዎቹ ይህንኑ ተረድተው ምርመራውን ማቋረጣቸውን አስታውቋል፡፡

በዘመን ባንክ በአካውንቱ ውስጥ ገንዘብ መኖሩን ተረጋግጦ፣ ችግሩ ሊፈጠር የቻለው በአካውንቱ ውስጥ ገንዘብ ባለመኖሩ ሳይሆን በፍርድ ቤት ውሳኔ በመታገዱ መሆኑን የሚገልጹ አሉ፡፡

ችግሩ የተፈጠረውም በዘመን ባንክ ስህተት መሆኑን የሚገልጹት ምንጮች፣ ባንኩ በጉዳዩ ሳይጠየቅ እንደማይቀር ተናግረዋል፡፡ የባንኩን ፕሬዚዳንት አቶ ኤርሚያስ እሸቱን በጉዳዩ ላይ ለማነጋገር ብንሞክርም፣ ‹‹በባንኩ ፖሊሲ መሠረት በደንበኞች ጉዳይ ላይ አስተያየት አንሰጥም፤›› በማለት ምላሽ ሰጥተዋል፡፡

አቶ ኤርሚያስ አመልጋ ወደተለመደው የሥራ ገበታቸው መመለሳቸውን ያስታወቀው አክሰስ ሪል ስቴት፣ በቀጣይ ሳምንታት ሥራውን አስመልክቶ ተጨማሪ መረጃዎችን ለደንበኞቹ ይፋ እንደሚያደርግ ገልጿል፡፡

አቶ ኤርሚያስ በኢትዮጵያ ቢዝነስ ውስጥ ተፅዕኖ ፈጣሪ ከሚባሉ ሰዎች ተርታ የሚመደቡ ናቸው፡፡ ከዚህ ቀደም አሜሪካ ውስጥ በተለያዩ ባንኮች ውስጥ በመሥራት የሚታወቁት አቶ ኤርሚያስ ኃይላንድ በመባል የሚታወቀውን ውኃ፣ ዘመን ባንክን፣ አክሰስ ሪል ስቴትና ሌሎች ተዛማጅ ቢዝነሶችን በመመሥረት ይታወቃሉ፡፡
http://www.ethiopianreporter.com

No comments:

Post a Comment