Sunday, February 19, 2012

በባሏ ጥቃት ዓይኖቿ የተጎዱት ነፍሰ ጡር የሕክምና ውጤት እየጠበቀች ነው


ነፍሰ ጡሯ በባለቤቷ በደረሰባት ድብደባ በዓይኖቿ፣ በአፍንጫዋና በመላ ሰውነቷ ላይ ከፍተኛ ጉዳት ደርሶባት በከፍተኛ ስቃይ ላይ እንደምትገኝ ቤተሰቦቿ አስታወቁ፡፡

በሁለት ዓይኖቿ ላይ የተፈጸመው ጥቃት የጉዳት መጠኑ ምን ያህል እንደሆነ የሕክምና ውጤት እየተጠባበቁ መሆኑን አስታውቀዋል፡፡ 

ወ/ሮ ፀዳለች አስረስ ጥር 29 ቀን 2004 ዓ.ም. ከምትሠራበት ዳሸን ባንክ ውላ ወደ ቤቷ ስትገባ፣ “እኔ የምልሽን የማትፈጽሚው ሆን ብለሽ ነው” በማለት ሠራተኛቸውንና የሁለት ዓመት ሕፃን ልጃቸውን ወደ ሱቅ በመላክ በፈጸመባት ጥቃት ጉዳት እንዳደረሰባት የሚናገሩት ቤተሰቦቿ፣ በሁለቱም ዓይኖቿ ላይ ከፍተኛ ጉዳት መድረሱንና ዓይኖቿ ማየት አለማየታቸውን ለማረጋገጥ ከዳግማዊ ምኒልክ ሆስፒታል ውጤት እተየጠባበቁ መሆናቸውን ተናግረዋል፡፡

አፍንጫዋ መሰበሩንና ሕክምና ብታገኝም ከፍተኛ ደም እየፈሰሳት መሆኑን የምትናገረው የተጐጂዋ እህት፣ የሁለት ወር ነፍሰ ጡር መሆኗንም ገልጻላች፡፡

ድርጊቱ ከተፈጸመባት ዕለት ጀምሮ ለንፋስ ስልክ ላፍቶ ክፍለ ከተማ ፖሊስ መረጃው እንደደረሰ፣ ነገር ግን ጥቃቱን አድርሷል የተባለው ተጠርጣሪው ባለቤቷ መሰለ ግርማ እስካሁን በቁጥጥር ሥር አለመዋሉን የተጐጂዋ እህት ገልጻለች፡፡ በቤተሰቦቹና በጓደኞቹ አማካይነት እርቅ እንዲፈጸም በተለያየ መንገድ ጥያቄ እያቀረበ መሆኑን የተጎጂዋ እህት አስረድታ፣ ፖሊስ ግለሰቡን እንዴት በቁጥጥር ሥር ማዋል እንዳልቻለ ግራ እንደገባት አስረድታለች፡፡ ፖሊሶች በተደጋጋሚ ሲጠየቁ የመያዥያ ትዕዛዝ ከፍርድ ቤት አውጥተው እየተከታተሉት መሆኑን እንደገለጹላቸው ተናግራለች፡፡

ባልና ሚስቶቹ ትዳር መሥርተው ልጅ ከወለዱ ሁለት ዓመታት እንዳለፋቸው የገለጸችው የተጐጂዋ እህት፣ ግንኙነታቸው ግን ከልጅነታቸው ከስድስተኛ ክፍል ጀምሮ ሁለቱም ከተወለዱበት ደቡብ ክልል ጀምጀም አውራጃ ቦሬ ከተማ ውስጥ መሆኑን ትናገራለች፡፡ ሁለቱም ውጤት አግኝተው ዩኒቨርስቲ ሲገቡ እሷ አምቦ እሱ ደግሞ ጅማ ቢደርሳቸውም፣ እሷ ወደ ጅማ ዩኒቨርሲቲ በፈቃዷ ተቀይራ ሁለቱም ከጅማ ዩኒቨርሲቲ መመረቃቸውንና በተለያዩ የዳሸን ባንክ ቅርንጫፎች እንደሚሠሩ አስታውቃለች፡፡

ትዳር መሥረተው አብረው መኖር ከጀመሩ ጊዜ አንስቶ ስምምነት እንደሌላቸው የገለጸችው የተጐጂዋ እህት፣ ተጐጂዋ እንደነገረቻት ባለቤቷ አደጋውን ያደረሰባት ምክንያት፣ እሷ ቀድሞ ከምትሠራበት የደንበኞች አገልግሎት የሥራ መደብ ተቀይራ ቢሮ ውስጥ ገብታ እንድትሠራ አለቃዋ እንደነገራት ትነግረዋለች፡፡ “አይ አይሆንም፤ ሂጅና መሥራት የምፈልገው ፊት ለፊት በሚሠራው የደንበኞች አገልግሎት ክፍል ነው በይውና በቀድሞ ቦታሽ እንድትሠሪ ጠይቂ፤” ይላታል፡፡ አለቃዋ ከእንግዶች ጋር ስለነበር ማናገር ባለመቻሏ የሥራ ሰዓት አብቅቶ ወደ ቤታቸው እንደሄደችና አለቃዋን እንዳላናገረች ትነግረዋለች፡፡ በዚህ ጊዜ “ይኼንን ያደረግሺው አውቀሽ ነው፤ ከዚያ ቦታ ለመቀየር ፍላጐት ስለሌለሽ ነው፤” በማለት ሕፃኑንና ሠራተኛቸውን ወደ ሱቅ በመላክ ጉዳቱን እንዳደረሰባት እንደነገረቻት እህትየው ገልጻለች፡፡

ድርጊቱን በማድረስ ወንጀል የተጠረጠረው የተጐጂዋ ባለቤት ለምን ሊያዝ እንዳልቻለ፣ ክትትሉስ በምን ሁኔታ ላይ እንዳለ የንፋስ ስልክ ላፍቶ ክፍለ ከተማ ፖሊስ መምርያን ለማነጋገር ቢሞከርም፣ ጉዳዩ በምርመራ ላይ መሆኑን ከመግለጽ ያለፈ ተጨማሪ መረጃ ማግኘት አልተቻለም፡፡  

No comments:

Post a Comment