Sunday, November 27, 2011

ከኔትወርክ ፍተሻ ጋር በተያያዘ ቻይናዊው የዜድቲኢ ባለሙያ የኢትዮ ቴሌኮም ኢንጂነሩን በስለት ወጋው




ዜድቲኢ የተባለው የቻይና የቴሌኮም ኩባንያ ከአዲስ አበባ በስተደቡብ 600 ኪሎ ሜትር ርቀት ላይ በሚገኘው በነገሌ ቦረና አካባቢ የተዘረጋው የቴሌኮም ኔትወርክ ጥራቱ ተቀባይነት እንደሌለው በመግለጽ የተሠራውን ሥራ ውድቅ ያደረገው የኢትዮ ቴሌኮም ኢንጂነር፣ ኔትወርኩን በዘረጋው የዜድቲኢ ቻይናዊ ባለሙያ በስለት ተወግቶ ጉዳት እንደደረሰበት፣ ለፕሮጀክቱ ቅርበት ያላቸውና ድርጊቱን ያዩ የዓይን እማኞች ለሪፖርተር ገለጹ፡፡ ድርጊቱ የተፈጸመው ባለፈው ሳምንት ዓርብ መሆኑን የገለጹት ምንጮች፣ የኢትዮ ቴሌኮም ኢንጂነር ለቻይናው ባለሙያ ክፍያ የሚያሰጠውን የተቀባይነት ሠርተፍኬት በመንፈጉ ምክንያት መሆኑን አረጋግጠዋል፡፡

‹‹የተዘረጋው ኔትወርክ ተቀባይነት እንደሌለውና የተቀባይነት ሠርተፍኬት ሊሰጠው እንደማይገባ ኢትዮጵያዊው ኢንጂነር ካብራራ በኋላ፣ በእሱና በቻይናው ባለሙያ መካከል ለረጅም ሰዓታት ውዝግብ ተፈጥሮ ነበር፤›› ሲሉ የገለጹት ምንጮች፣ ከውዝግቡ በኋላ የቻይናው ባለሙያ ኢንጂነሩን ደረቱ አካባቢ በስለታማ መሣርያ እንደወጋው አብራርተዋል፡፡

ኢንጂነሩ በስለቱ ከተወጋ በኋላ በአካባቢው በነበሩ ሠራተኞች አማካይነት በፍጥነት ሐዋሳ ከተማ ወደሚገኝ ሆስፒታል መወሰዱንና ለሦስት ቀናት ሕክምና ከተከታተለ በኋላ ባለፈው ማክሰኞ ከሆስፒታል መውጣቱን አስታውቀዋል፡፡

የኢንፎርሜሽንና የኮሙዩኒኬሽን ቴክኖሎጂ ሚኒስትሩ ዶክተሩ ደብረ ፅዮን ገብረ ሚካኤል በአገር አቀፍ ደረጃ 1.5 ቢሊዮን ዶላር በዜድቲኢ የሚዘረጋው ኔትወርክ የደረጃ ጥራቱ እንደሚፈተሽና ጥራቱ የተጠበቀ ካልሆነም ውድቅ እንደሚደረግ፣ በሚዘረጋው ኔትወርክ ጥራት ላይ ምንም ዓይነት ድርድር እንደማይደረግ ቀደም ሲል ለሪፖርተር መግለጻቸውን መዘገባችን ይታወሳል፡፡

የተዘረጋው የቴሌኮም ኔትወርክ አሁን በአገልግሎት ላይ ካለው ኔትወርክ ጋር ከመዋሀዱ በፊት፣ በሦስተኛ ወገን ጥብቅ ፍተሻ እንደሚደረግበት ሚኒስትሩ አስረግጠው ተናግረዋል፡፡

በተፈጠረው ያልተጠበቀ ክስተት የተገረሙ የኢትዮ ቴሌኮምና የዜድቲኢ ከፍተኛ አመራሮች ችግሩን በሰላም ለመፍታት እየተንቀሳቀሱ መሆናቸውን ምንጮች ጠቁመዋል፡፡ ችግሩን ለመፍታትም የዜድቲኢ ምክትል ኃላፊ አዲስ አበባ መግባታቸውም ታውቋል፡፡

ስማቸውን ለመግለጽ ያልፈለጉ አንድ የሕግ ባለሙያ ለሪፖርተር እንደገለጹት፣ በቻይናው ባለሙያ የተፈጸመው ድርጊት በመግደል ሙከራ ሊያስከስስ ይችላል፡፡

ከኢትዮ ቴሌኮም ኢንጂነሮች በተጨማሪ ገለልተኛ የሆነ ሌላ ኩባንያ 1.5 ቢሊዮን ዶላር እየተዘረጋ የሚገኘውን ኔትወርክ ጥራት በመፈተሽ ላይ ነው፡፡ የሚደርስበትን ውጤት በሁለት ወራት ውስጥ ያሳውቃል ተብሎ ይጠበቃል፡፡

የተፈጠረውን ችግር አስመልክቶ ከኢትዮ ቴሌኮም መረጃ ለማግኘት ያደረግነው ጥረት አልተሳካም፡፡




No comments:

Post a Comment