Wednesday, November 16, 2011

ሆስተሷ ስለተፈጸመባት ጥቃት ፍርድ ቤት ቀርባ መሰከረች “ልቤ ተሰብሯል” ሆስተስ አበራሽ ኃይላይ


ዓቃቤ ሕግ ለምስክሯ መሪ ጥያቄ ለማቅረብ በመዘጋጀት ላይ እንዳለ፣ ተጠርጣሪው ‹‹ሆድዬ ስለ እግዚአብሔር ብለሽ እውነቱን ተናገሪ›› በማለት ጮኾ ሲናገር፣ ፍርድ ቤቱ እሱን በማስጠንቀቅ እንዲቀመጥ ካደረገው በኋላ በእስረኞች ማቆያ ሳጥን ውስጥ ተቀምጦ ማዳመጥ ጀመረ፡፡ አበራሽ ስለተፈጸመባት ጥቃት፣ መቼ፣ እንዴትና በማንና በምን ሁኔታ እንደተፈጸመ ለፍርድ ቤቱ እንድታስረዳለት ጠየቃት፡፡

/ አበራሽ በተጠየቀችው መሠረት ስለተፈጸመባት ጥቃት ለፍርድ ቤቱ እንደገለጸችው፣ መስከረም 2 ቀን 2004 .. ከነበረችበት ቦታ እህቷ እየሸኘቻት ሳለ፣ ተጠርጣሪው ስልክ ደወለላት፡፡ ‹‹የት ነው ያለሽው?›› ብሎም ጠየቃት፡፡ ‹‹ወደ ቤቴ እየሄድኩ ነው፤ ስደርስ እደውልልሀለሁ፤›› አለችው፡፡ እቤቷ ስትደርስ ደወለችለት፡፡ ‹‹እየመጣሁ ነው›› አላት፡፡

ከምሽቱ ከአራት እስከ አራት ተኩል በሚሆን ጊዜ ውስጥ አቶ ፍስሐ እሷ በምትኖርበት ገርጂ ቁጥር 5 ኮንዶሚኒየም ቤት ውስጥ መድረሱን የገለጸችው / አበራሽ፣ አቶ ፍስሐ ገና ገብቶ ቁጭ ሲል ሲጋራ በመለኮሱ ‹‹ሳይነስ እንዳለብኝ ታውቃለህ፤ አጥፋልኝ፤›› ስትለው፣ ‹‹ዛሬ ለመጨረሻ ጊዜ ነው ሁለተኛ አላጨስም፤›› በማለት ሲጋራውን አጥፍቶ መቀመጡን ለፍርድ ቤቱ አስረድታለች፡፡

‹‹ተለያየን፣ ልጅም አልወለድንም፤›› ካላት በኋላ፣ በተቀመጡበት ፊት ለፊት በግድግዳ ላይ የተሰቀሉትን የእህቷንና የወንድሟን ፎቶግራፎችንና በቴሌቪዥን ላይ የተቀመጠውን የእናቷን ፎቶ እየተመለከተ፤ ‹‹የናትሽስ ይሁን፣ እኔ ከእህትና ከወንድምሽ በምን አንሼ ነው ፎቶዬ ያልተሰቀለው?›› በማለት ነገር ነገር ሲለው ‹‹ነገ በራሪ ስለሆንኩ ማረፍ አለብኝ፤ ሂድልኝ›› አለችው፡፡ ‹‹እሺ እሄዳለሁ›› በማለት ወደ መውጫው በር ከተራመደ በኋላ፣ ‹‹የመጨረሻ ስጦታ ይዤልሽ መጥቻለሁ›› በማለት ከኪሱ ሽጉጥ በማውጣት መጀመሪያ ወደ ግድግዳው፣ ቀጥሎ ወደ እርሷ በመደገን እንድትቀመጥ ትዕዛዝ ማስተላለፉን መስክራለች፡፡

‹‹ውይ ፊሽ እየቀለድክ ነው?›› ስትለው ‹‹ቁጭ በይ ብዬሻለሁ›› በማለት በያዘው ሽጉጥ ሰደፍ ግንባሯን ሲመታት ቁጭ ማለቷን የገለጸችው / አበራሽ፣ ቀጥሎ በእግሩና በእጁ ደጋግሞ ሲመታት፣ ራሷን ለመከላከል የሞት ሞቷን ስትይዘው፣ ሁለቱም ተያይዘው መውደቃቸውንና እሷ ከላይ እሱ ከታች መደራረባቸውን ለፍርድ ቤቱ አስረድታለች፡፡

ሽጉጡን ለመንጠቅ በተኙበት ትግል ብትጀምርም፣ አንገቷን አንቆ ስለያዛት ራሷን መቆጣጠር አቅቷት ራሷን ስትስት እንደለቀቃት የተናገረችው ምስክሯ፤ የቆየችበትን ሰዓት ባታውቀውም ስትነቃ ከፊት ለፊቷ ቆሞ ስለነበረ ከኪሱ ስለት ነገር አውጥቶ ግራ ዓይኗን እንደወጋትና ቀኝ ዓይኗን ሊደግማት ሲል በእጇ መከላከሏን ገልጻለች፡፡

ፀጉሯን ይዞ ከመሬት ጋር እንዳጋጫት፣ ቀኝ ዓይኗንም ደጋግሞ እንደወጋትና በእጁ ጣት የግራ ዓይኗን ወደ ውጭ ጎልጉሎ እንዳወጣው የመሰከረችው / አበራሽ፣ ራሷን ከሳተች በኋላ ወገቧንና የተለያዩ የሰውነት ክፍሎቿን በመምታት ሽጉጡን በእጇ አስጨብጧት መሄዱን ተናግራለች፡፡

በትዳር ቆይተው ከተፋቱ በኋላ ስለነበራቸው ግንኙነት ተጠይቃ እንዳስረዳችው፣ ከተፋቱ በኋላ በሠለጠነ መንገድ እህትና ወንድም ሆነው የመኖር ሐሳብ ስለነበራት እንዳልተራራቁ ገልጻ፣ እሱ ግን ስልክ ደውሎ ሲያጣት ወይም ሲነጋገሩ አለመግባባት ሲኖር ያስፈራራት እንደነበርም አስታውቃለች፡፡

በጳጉሜን 6 ቀን 2003 .. ከውጭ የመጡ ጓደኞቿ ጋብዘዋት ሲዝናኑ ደውሎላት ‹‹እንገናኝ›› ሲላት፣ ከጓደኞቿ ጋር መሆኗን ገልጻለት ‹‹አንገናኝም›› ስትለው ዝቶባትና አስፈራርቷት እንደነበር የተናገረችው ምስክሯ፣ የፈራቸው እንደደረሰባት ተናግራለች፡፡

ስለደረሰባት ጉዳት ከሐኪም የተነገራትን ሁኔታም ተጠይቃ በጭንቅላቷ ውስጥ ደም መፍሰሱን፤ ሁለቱም ዓይኖቿ ሙሉ በሙሉ መጥፋታቸውን፣ የቀኝ ዓይኗ ነርቭ መጎዳቱን፣ ወገቧ ብዙ መቆም እንደማያስችላት (የፊዚዮፔራፒ ሕክምና እየተደረገላት ነው) በግራ በኩል ያለው ሰውነቷ በሙሉ መደንዘዙን፣ ሦስት የእጆቿ ጣቶች መጎዳታቸውን ከሐኪሞቿ ማወቋንና ሕክምናዋን እንዳልጨረሰች በዝርዝር አስረድታለች፡፡

የተከሳሹ ጠበቆች ለደረሰባት ጉዳት እነሱም እንደሚያዝኑ ገልጸው፣ አቶ ፍስሐ ደውሎ እንደሚመጣ መፍቀዷን ወይም መከልከሏን፣ ከመጣ በኋላ በስንት ሰዓት መደባደብ እንደጀመሩ፣ መጀመሪያ የተነጋገሩት በሰላም ነው ወይስ አይደለም ጣቱን ዓይኗ ውስጥ ሲያስገባ ታውቃለች ወይስ አታውቅም? ሲያስገባ ይታያት ወይም አይታያት እንደሆነ፣ ፖሊስ ጠርቶ ሲመጣ ‹‹ፊሽ›› ያለችው ድምፁን በምን እንደለየችው፣ የሚሉና ሌሎችንም መስቀለኛ ጥያቄዎችን አቅርበውላታል፡፡

እንዲመጣ እንደፈቀደችለት፣ የመጣውም ከአራት እስከ አራት ተኩል ባለው ሰዓት ውስጥ መሆኑን፣ ትንሽ ቆይቶ ድብደባ መጀመሩን፣ ጣቱን በዓይኗ ውስጥ ሲያስገባ ያማት ስለነበር ይታወቃት እንደነበር፣ ጣቱን ሲከት ግን አለማየቷን፣ ከፖሊስ ጋር መጥቶ ፖሊስ ሲጠራት ‹‹ፊሽ ነህ›› ያለችው ሁልጊዜ ድምፁን እየቀያየረ ያናግራት ስለነበር እሱ መስሏት መሆኑንና ለሌሎችም ጥያቄዎች ምላሽ በመስጠት የምስክርነት ቃሏን አጠቃላለች፡፡

ፍርድ ቤቱ ምስክርነቷን ከጨረሰች በኋላ ተከሳሹ በሁለቱም ክሶች እንዲከላከል ብይን ሰጥቷል፡፡ የመከላከያ ምስክሮቹን ለመስማት ለህዳር 12 ቀን 2004 .. ተለዋጭ ቀጠሮ ሲሰጥ የተከሳሽ ጠበቆች ማመልከቻ አቅርበው ፍርድ ቤቱ ሰምቷቸዋል፡፡

ጠበቆቹ ባቀረቡት አቤቱታ የግል ተበዳይዋን (ወሮ አበራሽ) በመከላከያ ማስረጃነት ስለቆጠሯት፣ ረዘም ያለ ጊዜ ተሰጥቷቸው ወይም በአዳሪ እንድትሰማላቸው ሲጠይቁ፣ ፍርድ ቤቱ በሰጠው ምላሽ ምስክር ማሰማት የሚቻለው መጥሪያ ወስዶ በመጥራት በመሆኑ፣ እነሱም መጥሪያ አውጥተው ማስመስከር መብታቸው መሆኑን በመግለጽ፣ የቀጠሮው ቀን ግን እንደማይቀየር በማዘዝ ችሎቱ ተጠናቋል፡፡

/ አበራሽ ከፍርድ ቤት መልስ በሸራተን አዲስ የኢትዮጵያ ሴቶች ቅንጅት ማኅበር ባዘጋጀላት ጋዜጣዊ መግለጫ ላይ ተገኝታ፣ በተፈጸመባት አስከፊ ወንጀል ከጎኗ ለቆሙ ማኅበራት፣ ለመገናኛ ብዙኅን፣ እስካሁን ለወጣውና ወደፊትም ለሚቀጥለው የሕክምና ክፍያ ሙሉ ወጭ የቻሏትን ሼክ መሐመድ አሊ አል አሙዲን፣ ለኢትዮጵያ አየር መንገድና ለሌሎችም ምስጋና አቅርባ ‹‹እኔ ልቤ ተሰብሯል፤ የህሊና ስብራት እንዳይደርስብኝ ላጽናናችሁኝ ሁሉ እግዚአብሔር ከእኔ ዓይነት አስከፊ ሁኔታ ከነቤተሰቦቻችሁ ይጠብቃችሁ፤›› ብላለች፡፡
http://www.ethiopianreporter.com

No comments:

Post a Comment