Sunday, October 23, 2011

እነ ኤልያስ ክፍሌ የተመሠረተባቸው የአሸባሪነት ክስ እንዲሻሻል ትዕዛዝ ተሰጠ


ሕገ መንግሥቱንና ሕገ መንግሥታዊ ሥርዓቱን በተደራጀ የሸብር ድርጊት ለማፍረስ እንቅስቃሴ ሲያደርጉ ተደርሶባቸዋል በሚል በሽብር ወንጀል በኤልያስ ክፍሌና በአራት ተጠርጣሪዎች ላይ ከተመሠረቱት አራት ክሶች መካከል፣ ሁለተኛው እንዲሻሻል ፍርድ ቤት ጥቅምት 9 ቀን 2004 ዓ.ም. ትዕዛዝ ሰጠ፡፡
የፌዴራል ዓቃቤ ሕግ በሽብር ወንጀል ተጠርጣሪዎቹ ላይ ጳጉሜን 1 ቀን 2003 ዓ.ም. የመሠረተው ክስ፣ ጥቅምት 9 ቀን 2004 ዓ.ም. ለፌዴራል ከፍተኛ ፍርድ ቤት ሦስተኛ ወንጀል ችሎት ቀርቦ የተነበበ ሲሆን፣ በተከላካይ ጠበቆች በቀረበ ተቃውሞ ሁለተኛውን ክስ ዓቃቤ ሕግ አሻሽሎ እንዲያቀርብ ትዕዛዝ ሰጥቷል፡፡

በሽብር ወንጀል ተጠርጣሪዎቹ አቶ ኤልያስ ክፍሌ (በሌሉበት)፣ የኢትዮጵያ ብሔራዊ አንድነት ፓርቲ ሊቀመንበር አቶ ዘሪሁን ገብረ እግዚአብሔር፣ የአውራ አምባ ታይምስ ጋዜጣ ምክትል ዋና አዘጋጅ ውብሸት ታዬ፣ መምህርትና ዓምደኛ ርዕዮት ዓለሙና ሒሩት ክፍሌ ሲሆኑ፣ ጠበቆቻቸው እንዲሻሻል ጥያቄ ያቀረቡት ክስ ዓቃቤ ሕግ በሁለተኛነት ባቀረበውና ሁሉንም ተጠርጣሪዎችን በሚመለከተው ክስ ላይ፣ በፀረ ሽብርተኝነት አዋጅ ቁጥር 652/2001 አንቀጽ ሰባትን በመተላለፍ የሚለው ነው፡፡

እንደ ጠበቆቹ ተቃውሞ በፀረ ሽብርተኝነት አዋጅ ቁጥር 652/2001 አንቀጽ ሰባት ሥር ሁለት ንዑስ አንቀጾች መኖራቸውን ጠቅሰው፣ የትኛውም ተከሳሽ በየትኛው ንዑስ አንቀጽ እንደሚጠየቅ ስለማይገልጽ፣ በግልጽ መቀመጥ እንዳለበት ያቀረቡት ተቃውሞ በፍርድ ቤቱ ተቀባይነት አግኝቷል፡፡ በመሆኑም ዓቃቤ ሕግ አንቀጾቹን ለያይቶና አስተካክሎ እንዲያቀርብ ታዟል፡፡

ጥቅምት 9 ቀን 2004 ዓ.ም. የአምስቱንም የሽብር ወንጀል ተጠርጣሪዎች ክስ ማየት የጀመረው የፌዴራል ከፍተኛ ፍርድ ቤት ሦስተኛ ወንጀል ችሎት፣ ክሱን በንባብ ከማሰማቱ በፊት ተጠርጣሪዎቹ መኖራቸውን አረጋግጦ፣ አቶ ኤልያስ ክፍሌ በጋዜጣ ቢጠሩም ሊቀርቡ አለመቻላቸውን ዓቃቤ ሕግ በማስታወቁ በወንጀል ሕግ ቁጥር 163 መሠረት በሌሉበት እንዲታይ ወስኗል፡፡

ፍርድ ቤቱ በችሎት ለተገኙት ተጠርጣሪዎች የተከሰሱበትን የወንጀል ዝርዝር በንባብ ካሰማ በኋላ፣ በወንጀል ሕግ 130 መሠረት የተጠርጣሪዎቹ ጠበቆች ቅሬታ ካላቸው እንዲያቀርቡ ጠይቋል፡፡

ተቃውሞ እንዳላቸው የገለጹት የአቶ ዘሪሁን፣ የጋዜጠኛ ውብሸትና የሒሩት ጠበቃ ደርበው ተመስገን፣ የወንጀል ድርጊቶቹና የሕጉ አገላለጽ አይጣጣሙም ብለዋል፡፡ “ደጋፊ መረጃዎቹ ተጠርጣሪዎቹ ክሱን በግልጽ ተረድተው ለመከላከል በሚያስችል መልኩ አልቀረቡም፡፡ ተከሳሹ የተከሰሰበትን ወንጀል ለይቶና አውቆ መልስ ለመስጠት እንዲችል፣ እያንዳንዱ ክስ ወንጀሉንና ሁኔታውን በዝርዝር መግለጽ አለበት፡፡ የወንጀል ሕግ 12ን መመልከት ያስፈልጋል፤” ያሉት ጠበቃው፣ በተጠርጣሪ ተከሳሾቹ ላይ የቀረበው ክስ ከተጠቀሱት የፀረ ሽብርተኝነት ሕግ አንቀጾች ጋር የማይሄድና በጥቅሉ የቀረበ ነው ሲሉ አስረድተዋል፡፡ በወንጀል ሕግ አንቀጽ 111/1/ሐ መሠረት ወንጀሉ የተፈጸመበት ጊዜና ቦታ መገለጽ ቢኖርበትም፣ በክሱ ላይ ቀኑና ወሩ ባልታወቀበት ከ2003 ጀምሮ መባሉ ‹‹እኔ አልነበርኩም›› ብሎ ለሚከራከር አመቺ አይደለም ብለዋል፡፡

ዓቃቤ ሕግ በአንደኛ ክሱ ጥምረት በመፍጠር፣ የትብብር ስምምነት በመፈራረም፣ በጋራ የሽብር ስትራቴጂና ዕቅድ ላይ በመወያየት፣ የሥራ ክፍፍል በማድረግ የኤሌክትሪክ መስመሮችን ከጥቅም ውጭ ለማድረግ በመስማማት ከሚል ጥቅም አባባል በቀር እነማን የት እንደተፈራረሙ፣ የት ቦታና መቼ የጋራ ውይይት እንዳደረጉና እንደተስማሙ ስለማያመለክት በማለት ጠበቃው ተቃውመዋል፡፡

እንደ ጠበቃ ደርበው ተቃውሞ፣ ተከሳሾቹ ምን የሚባል የሽብርና የቅስቀሳ ጽሑፎች ከማን እንደተቀበሉ፣ ለማን እንዳሠራጩ፣ እነማን ያሉበትን የሽብር ቡድን እንዳደራጁ፣ ከየትኛው የሽብር ቡድን ገንዘብ እንደተቀበሉና  ማን ለተባለ የሽብር ቡድን መረጃ እንደሰጡ በቦታና በጊዜ ተለይቶ አልተጠቀሰም፡፡

የፀረ ሽብርተኝነት አዋጅ ቁጥር 652/2001 አንቀጽ 3(6) እና ወይም 4 ሥር የሚለው የዓቃቤ ሕግ ክስ በተፈጸመው ወንጀል እርግጠኛ አለመሆን ስለሚያሳይ፣ ተከሳሹ ለመከላከል በሚያስችል መልኩ በግልጽ አለመቀመጡን ጠበቃው አስታውቀዋል፡፡

ዓቃቤ ሕግ በሦስተኛ ክሱ በሁሉም ተከሳሾች ላይ የፀረ ሽብርተኝነት ሕግ አዋጅ ቁጥር 652/2001 አንቀጽ ዘጠኝን፣ በአማራጭም የወንጀል ሕግ አንቀጽ 684 (1) እና (2) መጥቀሱን የገለጹት ጠበቃው፣ በአዋጁ አንቀጽ ዘጠኝ እንደተገለጸው፣ በሽብርተኝነት ድርጊት የተገኘን ንብረት ስለመያዝና መገልገል የሚገልጽ ቢሆንም፣ ገንዘቡ በምን ዓይነት የሽብር ተግባር ከእነማን እንደተገኘ አለመገለጹን ጠቁመው፣ የወንጀል ሕግ አንቀጽ 684 (1) እና (2) ግን በወንጀል ድርጊት የተገኘን ገንዘብ ወይም ንብረት ሕጋዊ አስመስሎ ማቅረብን የሚመለከት ስለሆነ በሙስና በአደንዛዥ ዕፅ ወይም በመድኃኒት ዝውውር፣ በሕገወጥ የጦር መሣርያ ንግድና በሌላ ሕገወጥ ተግባር የተገኘ መሆኑን ክሱ እንደማያመላክት፣ ወይም የተጠቀሰው የወንጀል ወጤት አለመሆኑን እንደማያሳይ አብራርተዋል፡፡

የመምህርትና ጋዜጠኛ ርዕዮት ዓለሙ ጠበቃ ሆነው የቀረቡት ጠበቃ፣ ጠበቃ ሞላ ዘገዬ ተቃውሞ ካላቸው እንዲያስመዘግቡ ፍርድ ቤቱ ሲጠይቃቸው፣ የሌሎች ተከሳሾች ጠበቃ ደርበው ተመስገን ያስመዘገቡት የተቃውሞ ሐሳብ ለእሳቸው እንዲመዘገብላቸው ፍርድ ቤቱን በመጠየቅ አስመዝግበዋል፡፡

ዓቃቤ ሕግ ከጠበቆቹ የተነሳበትን የተቃውሞ ሐሳብ በሚመለከት በሰጠው ምላሽ፣ ለተጠቀሱት ክሶች ሁሉ ዝርዝር ማስረጃዎችን ማቅረቡን፣ የእያንዳንዱ ተጠርጣሪ ግንኙነትን መግለጹን፣ ተናግሮ ወቅቱና ጊዜው አልተጠቀሰም ለተባለው ተቃውሞ ‹‹ዓመተ ምህረቱ 2003 መሆኑ ተጠቅሷል፤ ወሩና ቀኑ ከመስከረም እስከ ነሐሴ ሊሆን ይችላል፤›› በማለት መልስ ሰጥቷል፡፡ ዓቃቤ ሕግ ዝርዝር ነገሮችን ወደፊት በማስረጃ የሚያሳይ መሆኑንም አስታውቋል፡፡


በጧቱ የችሎት ጊዜ ሊጠናቀቅ ያልቻለው የዓቃቤ ሕግና የተከሳሽ ጠበቆች የተቃውሞ ምልልስ ከሰዓት 8፡30 ሰዓት ላይ ቀጥሎ፣ ፍርድ ቤቱ በሰጠው ብይን ጠበቆች ጊዜና ቦታ አልተጠቀሰም ያሉትን፣ ከወንጀሉ ባህሪ አንፃር ፍርድ ቤቱ እንዳልተቀበለው ገልጾ፣ ተጠርጣሪዎች ያላቸውን የወንጀል ተሳትፎን በሚመለከት ዓቃቤ ሕግ በሚያቀርባቸው ማስረጃዎች የሚታይ መሆኑን ተናግሮ፣ ዓቃቤ ሕግ የሚያሻሽለውን ክስ ሰምቶ፣ የተጠርጣሪ ተከሳሾቹን የዕምነት ክህደት ቃል ለመቀበል ለጥቅምት 13 ቀን 2004 ዓ.ም. ተለዋጭ ቀጠሮ ሰጥቷል፡፡
http://www.ethiopianreporter.com/

No comments:

Post a Comment