Saturday, October 29, 2011

ቴዲ አፍሮ ኢትዮጵያዊውን ወጣት በ700 ሺህ ብር ከሞት አተረፈ


ወንድሜን ከሞት ወደ ህይወት መልሶልኛል አህት
ከሶስት አመታት በፊት መቀሌ የሚገኙትን ቤተሰቦቹን ተሰናብቶ ኑሮውን ለማሰነፍ ለስራ ወደ ፑንትላንድ ያመራው ኢትዮጵያዊ ወጣት አስመሮም ኃይለስላሴ እዛው ሆቴል ከፍቶ እየሰራ ነበር፡፡
ከባለቤቱ እና አንዲት ሴት ልጁ ጋር አንድ አመት ያህል እንደቆየም በታህሳስ 2002 ዓ.ም. አምስት የታጠቁ ሶማሊያውያን በሌሊት ለዝርፊያ ባለቤቱን ለመድፈር እና
ግድያ ለመፈፀም ግብግብ ይገጥሙታል፡፡በወቅቱም አብረውት ከነበሩ ኢትዮጵያውያን ጋር በመሆን ራሳቸውን ለመከላል በወሰዱት እርምጃ ከዘራፊዎቹ አንዱ ህይወቱ ያልፋል፡፡አብረውት የነበሩት ኢትዮጵያውያን አምልጠው ወደ ሃገራቸው ይመለሳሉ፡፡አስምሮም ግን ታስሮ ጉዳዩን ሲከታተል ይቆያል፡፡ቤተሰቦቹ እንደሚሉትም በአካባው የሚኖሩ ሶማሊያውያን አስመሮም ጥፋት እንደሌለበት እና በሰዓቱም ተኝቶ እንደ
ነበር ምስክርነታቸውን ሰጥተውለታል፡፡ሆኖም ምስክርነታቸው ተቀባይነት ባለማግኘቱ ከአንድ አመት እስር በኋላ በሞት እንዲቀጣ ተወሰነበት፡፡
አስመሮም በእስር ቤት ሳለ ሚስት በግብግቡ ወቅት ጉዳት የደረሰባትን የሰባት ሴት ልጇን ይዛ ወደ ኢትዮጵያ የተመለሰች ሲሆን ታዳጊዋ ላይ የደረሰው ጉዳት ከፍተኛ ስለነበር ህይወቷ አልፏል፡፡የልጇን መሞት እና በባለቤቷ ላይ ሞት መፈረዱን መቋቋም ያቃታት ባለቤቱ በአሁኑ ሰዓት የት እንዳለች እነደማይታወቅ የአስመሮም እህት ሉዓም ኃይለስላሴ ለአዲስ አድማስ ተናግራለች፡፡
እህቱ እንደምትለው ወንደሟ ከታሰረ ሁለት አመት ሆኖታል፡፡ጉዳዩም ፑንትላንድ ውስጥ ቦሳሶ ከተማ ሲታይ ቆይቶ በከተማዋ ያ የጎሳ አባላት በሞት እንዲቀጣ ይወስናሉ፡፡የሞት ቅጣቱ የሚነሳለት ደግሞ 700ሺህ የኢትዮጵያ ብር ወይም ወደ 40ሺህ ዶላር አካባቢ ሲከፍል ብቻ እንደሆነ ውሳኔ ያስተላልፋሉ፡፡
ሁኔታው እጅግ ያስጨነቃቸው ቤተሰቦቹ በተለያየ ጊዜ በርካታ ደብዳቤዎችን ለውጭ ጉዳይ መስሪያ ቤት በመፃፍ መንግስት ዲፕሎማሲያዊ ጥረት በማድረግ የወጣቱን ህይወት እንዲያተርፍላቸው ቢማፀኑም ምላሽ ሳያገኙ መቅረታቸውን የወጣቱ እህት ለአዲስ አድማስ ገልፃለች፡፡
በዚህ ሁኔታ ውስጥ እያሉ ጥቅምት 7 ቀን 2004 ዓ.ም. ወጣት አስመሮም ቤተሰቦቹን እንዲሰናት በማለት አሳሪዎቹ ስልክ ወደ ቤተሰቦቹ እንዲደወል ያደርጋሉ፡፡በተደወለው ስልክም እስከ አርብ መስከረም 17 ቀን ድረስ ገንዘቡን መክፈል ካልቻለ የሞት ፍዱ ተፈፃሚ እንደሚሆን ተናግሮ የደህና ሁኑ መልዕክት በማስተላለፍ ቤተሰቦቹን ይሰናበታል፡፡
እህቱ እንደተናገረችው ቅጣቱ ፍትሃዊ ባለመሆኑ ተፈፃሚ እንዳይሆን የቻልንውን ሁሉ ሞከርን የሞት ፍርዱ ሊፈፀም ሁለት ቀናት ብቻ ሲቀሩት የውጭ ጉዳይ መስሪያቤት ሰራተኞች ምናልባት በስራ ጫና ወይም ከሱ የባሱ ጉዳዮችን ሲፈፅሙ አቤቱታችንን አልሰሙም ይሆናል በሚል አስበን የመጨረሻ እድል ለመሞከር ጉዳዩን ለሪፖርተር ጋዜጣ አስረዳን እነሱም ዜናውን ረቡዕ አወጡት፡፡እስከ ሃሙስ ማታም ምንም የተለወጠ ነገር አልነበረም፡፡ሃሙስ ምሽት ላይ ግን አንድ ስልክ ተደወለልኝ፡፡አንድ ሰው ገንዘቡን ከፍሎ የወንድማችሁን ህይወት ሊታደግ ነውና ነገ ትገናኛላችሁ፡፡የሚል ነበር ስትል ሁኔታውን ታስረዳለች፡፡
እህቱ እንደምትለው ቤተሰቦቹ የጠበቁት የመንግስት አካላት ጋዜጣውን አይተው ምላሽ ይሰጡናል ብለው እንጂ አንድ ግለሰብ ገንዘቡን ከፍሎ ያስለቅቅልና የሚል ግምት አልነበራቸውም፡፡በትናንትናው እለትም የወንድሟ መትረፍ እንጂ የወንድሟን ህይወት ለመታደግ ያሰበው ግለሰብ ማንነት ሳያስጨንቃት በደስታ እና በሲቃ ተውጣ የተባለው ቦታ ስትሄድ ገንዘቡን ከፍሎ የወጣቱን ህይወት ለመታደግ የወሰነው ግለሰብ አርቲስ ቴዎድሮስ ካሳሁን (ቴዲ አፍሮ ) መሆኑን ትረዳለች፡፡
ገንዘቡን የሰጠኝ በቼክ ነው ይህንን ያደረኩት እኔ ሳልሆን እግዚአብሄር ነው፡፡አይዞሽ ተፅናኚ ብሎ 700 ሺህ ብር የያዘ ቼክ  ሲሰጠኝ ማመን አልቻልኩም ምን እንደምናገርም አላውቅም ብቻ እኔ ሰው ነኝ ግን በእግዚአብሄር እና በቤተሰቦቼ ስም ስም እጅግ አድርጌ አመሰግነዋለሁ፡፡ብላለች፡፡አክላም ድሮም ቢሆን ቴዲን በጣም እወደው ነበር አሁን ደግሞ በጣም ወደድኩት ብላለች፡፡
ገንዘቡን ካገኘች በኋላም ስለ ገንዘቡ አከፋፈል እና አስመሮም ከእስር ተለቆ ወደ አገር ስለሚመለስበት ሁኔታ ከውጭ ጉዳይ መስሪያ ቤት ጋር ቤተሰቦቹ ቤተሰቦቹ እየተነጋገሩ መሆኑን በመግለፅ ቴዲ አፍሮ የሰጣትን ቼክ በዛሬው እለት መንዝራ በሚኒስቴር መስሪያ ቤቱ በኩል ገንዘቡ ተከፍሎ ወንድሟ ከእስር እንዲለቀቅ ጥረት በማድረግ ላይ መሆኗን ገልፃልናለች፡፡
ወጣት አስመሮምን በተመለከተ ወገናችንን ከሞት እናድን በሚል ቤተሰቦቹ እና ጓደኞቹ በራሪ ወረቀት ፅፈው በድረ ገፅ የልመና ድምፃቸውን ሲያሰሙ መቆየታቸውን በመግለፅ በመጨረሻ ቴዲ አፍሮ ደረሰልን ብለዋ-ቤተሰቦቹ፡፡ 

አዲስ አድማስ ጋዜጣ

No comments:

Post a Comment