Friday, July 22, 2011

Ethiopia plans a new stadium

የአዲስ አበባ ከተማ ከንቲባ ኩማ ደመቅሳ ከ23 ዓመታት በኋላ ቦሌ መድኃኒዓለም አካባቢ የሚገኘው 65 ሔክታር መሬት በአስቸኳይ እንዲታጠርና በቦታው ላይ የሚገኙ 543 ቤቶች እንዲፈርሱ ትዕዛዝ መስጠታቸውን ምንጮች አመለከቱ፡፡
በዚህ ቦታ ላይ ዘመናዊ ስታዲዮም ለመገንባታ እንቅስቃሴ ተጀምሯል፡፡

በቦሌ ክፍለ ከተማ ከ22 ማዞርያ ወደ ቦሌ መድኃኒዓለም በሚወስደው መንገድ ላይ የሚገኘው ሰፊ ቦታ ለስታዲዮም ግንባታ እንዲውል የተወሰነው፣ በወታደራዊው መንግሥት የሥልጣን ዘመን ቢሆንም ላለፉት 23 ዓመታት ውሳኔው ተግባራዊ መሆን ሳይችል ቆይቷል፡፡

በወቅቱ የአገሪቱ ፕሬዚዳንት የነበሩት ሌተና ኮሎኔል መንግሥቱ ኃይለ ማርያም በ1980 ዓ.ም. 15ኛው የምሥራቅና የመካከለኛው አፍሪካ የእግር ኳስ ውድድር አዲስ አበባ ላይ ተካሂዶ የኢትዮጵያ ብሔራዊ ቡድን የዚምባቡዌ አቻውን በመለያ ምቶች አሸንፎ ዋንጫ ሲወስድ፣ ከ100 ሺሕ ሰው በላይ የሚይዝ ስታዲዮም እንደሚገነባ ቃል ገብተው ነበር፡፡

በጊዜው በርካታ ተመልካቾች ስታዲዮሙ በመሙላቱ ምክንያት ጨዋታውን ለመከታተል አልተቻላቸውም ነበር፡፡ ከሁለት አስርት ዓመታት በኋላ በዚህ ቦታ ላይ የሚገኙት ነዋሪዎች ሙሉ በሙሉ ተነስተው የብሔራዊ ስታዲዮሙ ግንባታ እንዲጀመር ከንቲባው ትዕዛዝ መስጠታቸውን የተገኘው መረጃ ያመለክታል፡፡

በጉዳዩ ላይ የፌዴራል ስፖርት ኮሚሽን ከአስተዳደሩ ጋር በቅርብ ሆኖ እየሠራ የሚገኝ ሲሆን፣ ከንቲባው በቅድሚያ ለግንባታው የተወሰነው ቦታ እንዲታጠር አዘዋል፡፡ በዚህ ውሳኔ መሠረት ኮሚሽኑ በ60 ሺሕ ብር ወጭ አጥር እያሳጠረ ይገኛል፡፡

ቦታው ከታጠረ በኋላ በቦታው ላይ ይኖሩ የነበሩ ሰዎች እንዲነሱ እንደሚደረግ ታውቋል፡፡ ኮሚሽኑ ለሚያካሂደው ግንባታ የዲዛይን ሥራ የሚሠራ የአማካሪ ድርጅት ለመምረጥ በቅርቡ ጨረታ እንደሚወጣ፣ የኮሚሽኑ የስፖርት ማዘውተርያዎችና ተቋማት የሥራ ሒደት ዳይሬክተር አቶ ሀብታሙ አበበ ለሪፖርተር ገልጸዋል፡፡

‹‹ለዲዛይን ሥራ በጀት ተይዞልናል፤›› ሲሉ አቶ ሀብታሙ ጨምረው ገልጸዋል፡፡ ነገር ግን በቦታው ላይ የሚገኙ ነዋሪዎች ቅሬታ እያነሱ ነው፡፡ የቦሌ ክፍለ ከተማ ባለፈው ዓመት ባካሄደው ጥናት በቦታው ላይ የሚገኙ ነዋሪዎችን በሦስት ይከፍላል፡፡

እነሱም ካሳ የተከፈላቸው፣ ካሳ ተከፍሏቸው ያልተነሱና በሕገወጥ መንገድ የሰፈሩ ይላቸዋል፡፡ አስተዳደሩ ይህንን ቦታ ለኮሚሽኑ ለማስረከብ እንቅሰቃሴ የጀመረው በ1997 ዓ.ም. በመሆኑ ካሳ የተከፈላቸውም በዚያን ወቅት ነው፡፡ ነገር ግን አብዛኛዎቹ አልተነሱም፡፡ ከዚያም በኋላ በቦታው ላይ ሰፍረዋል የሚባሉትም ነዋሪዎች ካርታ በሕጋዊ መንገድ እንደተሰጣቸው በመግለጽ አስተዳደሩ ችግራቸውን ግንዛቤ ውስጥ እንዲከተው እየጠየቁ ነው፡፡

በአካባቢው ከሚገኙ የንግድ ድርጅቶች መካከል አንደኛው ድርጅት ይዞታውን ለኢትዮጵያ ንግድ ባንክ አስይዞ ለመበደር የሚያደርገው ጥረት አንዲቆም መደረጉን ኮሚሽኑ አስታውቋል፡፡ የድርጅቱ ባለቤትም ካሳ እንደማይፈልጉና በቦታው ላይ ልማት ማካሄድ የሚያስችል አቅም ያላቸው በመሆኑ ቅድሚያ እንዲሰጣቸው ከሚጠይቁት መካከል ይገኛሉ፡፡

ኮሚሽኑ የብሔራዊ ስታዲዮም ግንባታ አካል የሆነውን የስፖርት አካዳሚ ግንባታ በ200 ሚሊዮን ብር በዚሁ አካባቢ እየገነባ ነው፡፡ ይህ አካዳሚ እየተገነባ ያለው በቀለበት መንገድ በኩል በአራት ሔክታር መሬት ላይ ነው፡፡ የስፖርት አካዳሚው በአትሌቲክስ፣ በመረብ ኳስና በእግር ኳስ ስፖርቶች ለባለሙያዎች ሥልጠና እንዲሰጥ ታቅዷል፡፡

በአሁኑ ወቅት 85 በመቶ ግንባታው የተጠናቀቀ ሲሆን፣ ከአንድ ዓመት በኋላ ግንባታው ከሚጀመረው ብሔራዊ ስታዲዮም ጋር ተዳምሮ የአገሪቱን ስፖርት አንድ ደረጃ እንደሚያሸጋግረው እምነታቸው መሆኑን ባለሙያዎች ይገልጻሉ፡፡

No comments:

Post a Comment